በአማራ ክልል የተቋረጠው የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲጀምር ተጠየቀ
መስከረም 04፣ 2016
1. መንግስት በአማራ ክልል የተቋረጠውን የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲያስጀምር በርካታ ድርጅቶች የተሳተፉበት ጥምረት ጠይቋል። ጥሪውን ያቀረቡት ከ300 በላይ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች አባልየሆኑበት የኪፕኢትኦን (#KeepItOn) ንቅናቄ እንዲሁም 48 ፈራሚ ድርጅቶች ናቸው። ጥሪውን አስመልክቶ በተሰጠው መግለጫ በግጭት ወቅት የኢተርኔት ኣአገልግሎትን ማቋረጥ ዜጎች አስፈላጊ መረጃ የሚያገኙበትን አግባብ እንደሚገድብ ተገልጿል።
2. ዜጎች በማህበራዊ ሚዲያ ከሚሰራጩ ሀሰተኛ የጤና መረጃዎች እና ከሚያስከትሏቸው የጤና አደጋዎች እራሳቸውን እንዲጠብቁ የጤና ሚንስቴር በትናትናው ዕለት ባወጣው መግለጫ አሳስቧል። ሚንስቴሩ በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች በተለይም በቲክቶክ ሀሰተኛ የጤና መልእክቶች በብዛት በመሰራጨት ላይ እንደሚገኙም ገልጿል። መረጃ የሚያሰራጩትም “ሃላፊነት የጎደላቸው፣ የጤና ሙያ ሳይኖራቸዉ የጤና ሙያዊ ምክር እንሰጣለን” በሚሉ ሰዎች መሆናቸውን አስታውቋል። የጤና መረጃዎችን ከትክክለኛ የመረጃ ምንጭና ከጤና ባለሙያ ብቻ ማግኘት እንደሚገባም አሳስቧል።
3. ማህበራዊ ሚዲያ አገልግሎት የሚሰጡ ኩባንያዎች በመጭው የፈረንጆች ዓመት በበርካታ ሀገራት በሚደረጉ ምርጫዎች አንጻር የሚሰራጩ ሀሰተኛ መረጃዎችን ለመቆጣጠር በቂ ዝግጅት አላደረጉም ሲል ግሎባል ኮሊዥን ፎር ቴክ ጀስቲስ (Global Coalition for Tech Justice) የተባለ ዓለም አቀፍ ጥምረት ወቀሰ። የሲቪክ ማህበራት መሪዎችን እና በቴክኖሎጅ ሳቢያ ጉዳት የደረሰባቸውን ሰዎች ያሰባሰበው ይህ ጥምረት በተለይ ኩባንያዎቹ በተለያዩ ቋንቋዎች የሚሰራጩ ሀሰተኛ መረጃዎችን ለመቆጣጠር ያላቸውን ዝግጅት ተችቷል። ጥምረቱ በምርጫዎች አኳያ ኩባንያዎቹ ያደረጉትን ዝርዝር ዝግጅት ይፋ እንዲያደርጉ ጠይቋል። በፈረንጆቹ2024 ዓ.ም 2 ቢሊዮን ገደማ ሰዎች የሚሳተፉባቸው ከ50 በላይ ምርጫዎች በዓለም ዙሪያ እንደሚደረጉ ጥምረቱ አስታውሷል።
በዚህ ሳምንት ያቀረብናቸው መረጃዎች እና የቴሌግራም ሊንኮቻቸው፥
– በሰኞ መልዕክታችን ያለፈውን ዓመት ከሀሠተኛ መረጃ ስርጭት አኳያ መለስ ብለን ቃኝተን በአዲሱ አመት ልናደርገው የሚገባን ጥንቃቄ ተመልክተናል:
https://t.me/ethiopiacheck/2180
ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ
ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::