“ከኢትዮጵያ አየር መንገድ የቦርድ ሰብሳቢነት ከለቀቅሁ በኋላ ለየትኛውም ሚዲያ ማብራሪያ አልሰጠሁም”— አቶ ግርማ ዋቄ ለኢትዮጵያ ቼክ

ሰኔ 07፣ 2015 ዓ.ም

አቶ ግርማ ዋቄ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ የቦርድ ሰብሳቢነት መልቀቅቸውን ተከትሎ የእርሳቸውን ንግግር የያዙ አጫጭር ቪዲዮውች በቲክቶክ ሲጋሩ ተመልክተናል።

ከቪዲዮዎቹ ጋር “አቶ ግርማ ዝምታቸውን ሰበሩ” እና “አቶ ግርማ ዋቄ እንዲህ ብለዋል” የሚሉ ርዕሶች ይነበባሉ። በቪዲዮዎቹ የአስተያየት መስጫ ቦታ ሀሳባቸውን ያስቀመጡ በርከት ያሉ የቲክቶክ ተጠቃሚዎችም የአቶ ግርማ ንግግር አዲስ እንደመሰላቸው አስተውለናል።

ሆኖም ባለፉት ቀናት በቲክቶክ በመጋራት ላይ የሚገኙት ቪዲዮዎች የቆዩ መሆናቸውን ኢትዮጵያ ቼክ አረጋግጧል።

ቪዲዮዎቹ የተወሰዱት አቶ ግርማ ከፋና ብሮድካስቲግ ጋር ከወራት በፊት ካደረጉት ቃለምልልስ ተቆርጠው የተወሰዴ ሲሆን ትክክለኛውን ቪዲዮው ይህን ማስፈንጠሪያ በመከተል ማግኘት ይቻላል:
https://youtu.be/8qtnqP1fAGk

አቶ ግርማ የተጋሩት ቪዲዮዎች የቆዩ መሆናቸውን ለኢትዮጵያ ቼክ ያረጋገጡ ሲሆን “ከኢትዮጵያ አየር መንገድ የቦርድ ሰብሳቢነት ከለቀቅሁ በኃላ ለየትኛውም ሚዲያ ማብራሪያ አልሰጠሁም” በማለት ገልጸዋል።

የአየር መንገዱ የቦርድ ሰብሳቢ ሆነው ላለፈው ሁለት ዓመት ተኩል ሲያገለግሉ የነበሩት አቶ ግርማ ዋቄ ከሰኔ 1 ቀን 2015 ዓ/ም ጀምሮ የኢትዮጵያ አየር ኃይል አዛዥ በሆኑት ሌተናንት ጄኔራል ይልማ መርዳሳ መተካታቸውን አየር መንገዱ ባወጣው መግለጫ ማስታወቁ ይታወቃል።

አቶ ግርማ ከዚህ ቀደም የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈጻሚነትን እና የአመራር ቦርድ አባልነትን ጨምሮ በተለያዩ ኃላፊነቶች ተቋሙን እንዳገለገሉ በመግለጫው ተገልጿል።

ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ

    ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::