የጣልያኗ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሜሎኒ የስንዴ ነዶ ይዘው የሚታዩበት ምስል በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በቅንብር የተሰራ ነው

የጣልያኗ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሜሎኒ የስንዴ ነዶ ይዘው የሚታዩበት ምስል በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በቅንብር የተሰራ ነው

የካቲት 11፣ 2018

/ኢትዮጵያ ቼክ/- በቅርቡ ለጣሊያን-አፍሪካ ጉባኤ ኢትዮጵያን የጎበኙት የጣልያኗ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሜሎኒ የብልፅግና ፓርቲ የምርጫ ምልክት የሆነውን እና በቅርቡ ይፋ የሆነውን የስንዴ ነዶ ይዘው የሚያሳይ ምስል እና ቪዲዮ በማህበራዊ ትስስር ገጾች እየተጋራ ይገኛል።

በምስሉ እና ቪዲዮው ጠቅላይ ሚንስትሯ የስንዴ ነዶዉን ይዘው ከጠቅላይ ሚንስትር ዓቢይ አህመድ ጎን ቆመው ይታያል።

ይህን ምስል/ቪዲዮ ካጋሩ የፌስቡክ ገጾች መካከል ‘Ethiopian Voice’ የሚል ስም እና ከ493 ሺህ በላይ ከታዮች ያሉት ገጽ አንዱ ነው። ይሁን እንጂ ኢትዮጵያ ቼክ በምስሉ ላይ ባደረገዉ ማጣራት ምስሉ በቅንብር የተሰራ መሆኑን አረጋግጧል።

ይህ ምስል ሁለቱ መሪዎች እጅ ለእጅ ተጨባብጠው የተነሱትን ፎቶ ይዘት በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) መተግበርያዎች መቀየር የተሰራ ሲሆን ትክክለኛው ምስልም በጠቅላይ ሚንስትር ዓቢይ አህመድ የተረጋገጠ የፌስቡክ ገጽ ላይ ተጋርቶ ነበር፡ https://www.facebook.com/share/p/1ReKaaYatu/?mibextid=wwXIfr

ኢትዮጵያ ቼክ ምስሉን ‘SynthID Detector’ የተሰኘዉን የጉግል መሳሪያዎችን በመጠቀም የተፈበረኩ እና የተቀናበሩ ምስሎች እና ቪዲዮዎች መመርመሪያ መሳሪያ በመጠቀም ባደረገዉ ማጣራት ምስሉ ጉግል ኤአይ (Google AI) በመጠቀም የተቀናበረ እንደሆነ ተመልክቷል።

‘Fake Image Detector’ የተሰኘው የተቀናበሩ ምስሎች መመርመሪያ ድረ-ገጽም ምስሉ የተፈበረከ ወይም ይዘቱ የተለወጠ እንደሆነ አረጋግጧል።

በተጨማሪም የምስሉን የተለያዩ ክፍሎች ላይ ባደረግነዉ ጥልቅ ምልከታ ምስሉ የተቀናበረ መሆኑን የሚያመላክቱ ስህተቶችን ተመልክተናል።

ብልጽግና ፓርቲ የቀጣዩ ምርጫ መወዳደሪያ ምልክቱ የስንዴ ነዶ እንደሆነ ባለፈው ሳምንት ይፋ ማድረጉ ይታወቃል።

በሌላ በኩል የጣልያኗ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጊያ ሜሎኒን የኢትዮጵያ ቆይታ በተመለከተ ጠ/ሚ ዓቢያ በፌስቡክ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ “የጠቅላይ ሚኒስትር ሜሎኒ ጉብኝት በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በኢነርጂ፣ በመሠረተ ልማት፣ በግብርና እና በፈጠራ ዘርፎች የቀጠለውን ትብብራችን ለማጠናከር ያለንን የጋራ ቁርጠኝነት የሚያረጋግጥ ነው” ብለዋል።

ኢትዮጵያ ቼክ

ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ

    ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::