ይህ የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እንደፃፈው የሚያሳይ ደብዳቤ ትክክለኛ ነው

ይህ የገንዘብ ሚኒስቴር ለትግራይ ክልል ግዜያዊ አስተዳደር እንደፃፈው የሚያሳይ ደብዳቤ ትክክለኛ ነው

ጥቅምት 29፣ 2018

ባለፉት ሁለት እና ሶስት ቀናት አንድ በገንዘብ ሚኒስቴር ተፃፈ የተባለ ደብዳቤ ማህበራዊ ሚድያ ላይ በስፋት ሲሰራጭ ተመልከተናል።

ደብዳቤው በገንዘብ ሚኒስቴር እንደተፃፈ የሚታይ ሲሆን በሚኒስቴሩ የትሬዠሪ እና የመንግስት ሂሳብ መምሪያ ሀላፊ በሆኑት ግለሰብ የተፈረመ ነው።

ደብዳቤው “ለትግራይ ክልል ግዜያዊ አስተዳደር ፋይናንስ የሀብት ማስተባበርያ ቢሮ በ2018 በጀት አመት የጥቅምት ወር የበጀት ድጋፍ ብር 2,013,471,609.40 (ሁለት ቢልዮን አስራ ሶስት ሚሊዮን አራት መቶ ሰባ አንድ ሺህ ስድስት መቶ ዘጠኝ ብር ከአርባ ሳምቲም) ጥቅምት 12 ቀን 2018 በተፃፈ ደብዳቤ እንዲተላለፍ መላካችን ይታወሳል” ይላል።

በተጨማሪም “ሆኖም ከላይ የተጠቀሰውን ገንዘብ አስተካክለን መላክ በማስፈለጉ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ወደ ኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ እንዲመልስ እንጠይቃለን” ይላል።

ይህ ደብዳቤ ማህበራዊ ሚድያ ላይ መሰራጨት ከጀመረ አንስቶ በርካቶች ሀሰተኛ እንደሆነ ሲገልፁ ሌሎች ደግሞ ትክክለኛ እንደሆነ ሲያነሱ ነበር።

ኢትዮጵያ ቼክ በዚህ ዙርያ ባደረገው ማጣራት ደብዳቤው ትክክለኛ መሆኑን አረጋግጧል።

በዚህ ዙርያ ያነጋገርናቸው የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሺዴ ጉዳዩ “የቴክኒክ ጉዳይ ነው” ብለው አጭር ምላሽ ከሰጡን በኋላ “ችግር የለውም” በማለት ደብዳቤው ትክክለኛ ለመሆኑ ፍንጭ ሰጥተዋል።

በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ቼክ ያነጋገራቸው ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ አንድ ስለ ደብዳቤው ትክክለኛነት እውቀት ያላቸው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሀላፊ ማረጋገጫ ለኢትዮጵያ ቼክ ሰጥተዋል።

“ደብዳቤው ትክክከኛ ነው፣ በባንካችን የተፃፈ ነው። ጉዳዩ አንድ የተሰራ መጠነኛ የሂሳብ ግድፈት ስላለ እሱን ለማስተካከል ነው” በማለት ተናግረዋል።

አንዳንድ የማህበራዊ ሚድያ ተጠቃሚዎች የደብዳቤው መፃፍ ከሰሞኑ በፌደራል መንግስት እና ትግራይ ውስጥ ባሉ ሀይሎች መሀል እየተካረረ ከመጣው ውጥረት ጋር የተያያዘ መሆኑን ሲጠቅሱ ተመልክተናል።

ኢትዮጵያ ቼክ!

ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ

    ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::