ይህ በአዲስ አበባ ከተማ የተደረገ የተኩስ ልውውጥ ነው ተብሎ የተጋራ ቪድዮ አሳሳች ነው

ጳጉሜን 05፣ 2016 ዓ.ም
ከ10,000 በላይ ተከታዮች ያሉት እና ‘Abdikarin Dahir’ የሚል መጠሪያ ያለው የኤክስ/ትዊተር አካውንት በአዲስ አበባ ከተማ አልፎ አልፎ የተኩስ ድምጽ እንደሚሰማ የሚገልጹ ሪፖርቶች እየወጡ እንደሆነ የሚገልጽ መልዕክት ማጋራቱን ተመልክተናል።
አካውንቱ ጨምሮም በፋኖ ሀይሎች ጥቃት መድረሱን በመጥቀስ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት አካባቢውን ለመቆጣጠር እየሞከረ ነው ብሎ አስፍሯል።
ከመልዕክቱ ጋርም ቪዲዮ ያያዘ ሲሆን በቪዲዮው ላይ ወታደሮች ሲተኩሱ ይታያል። ይህንን መልዕክትና ቪዲዮ በተለይ በሱማሊያ ጉዳይ የሚጽፉ በርካታ የኤክስ ተጠቃሚዎች መልሰው ሲያጋሩት አስተውለናል።
ሆኖም ኢትዮጵያ ቼክ ባደረገው ማጣራት ከላይ የተጠቀሰው አካውንት ያጋራው ቪዲዮ የቆየና ከሌላ ቦታ የተወሰደ መሆኑን አረጋግጧል። ቪዲዮው የተቀረጸው በ2015 ዓ.ም ሚያዚያ ወር መጨረሻ በጎንደር ከተማ ከአማራ ክልል ልዩ ሃይል መፍረስ ጋር በተያያዘ ተቀስቅሶ በነበረ አለመረጋጋት ወቅት ነው።
በወቅቱ ቪዲዮው በበርካታ የማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች ተጋርቶም ነበር። ቪዲዮውን ካጋሩት መካከል ይህ ይገኝበታል: https://www.facebook.com/reel/798676867971478
ከአውድ ውጭ ተወስደው የሚጋሩ ቪዲዮዎች ለሀሰተኛ እና አሳሳች መረጃዎች ሊያጋልጡን ስለሚችሉ ከማጋራታችን በፊት ተገቢዉን ማጥራት እናድርግ።
ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ
ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::
