የኤርትራን ዋና ከተማ አስመራን ያሳያል በሚል ማህበራዊ ሚድያ ላይ የተሰራጨው ይህ ምስል የተሳሳተ ነው

የካቲት 11፣ 2018
/ኢትዮጵያ ቼክ/- በቅርብ ግዜያት በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መሀል እየተካረረ የመጣውን ውጥረት ተከትሎ በርካታ መልዕክቶች በፅሁፍ፣ በቪድዮ፣ በምስል እንዲሁም በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) በታገዙ ምርቶች በደጋፊዎቻቸው አማካኝነት እየተሰራጩ ይገኛሉ።
ከእነዚህም መሀል ‘ታዬ ቦጋለ አረጋ’ በመባል የሚታወቁት ግለሰብ ‘እነ እንቶኔ የሚናፍቋት ኤርትራ፤ የድሮዋ አራት ኪሎ እህት ከተማ’ ከሚል ፅሁፍ ጋር አስመራ ከተማን እንደሚያሳይ ቀጥተኛ ባልሆነ መልኩ የገለፁበትን ፅሁፍ አስተያየት መስጫ ላይ ለጥፈው ተመልክተናል።
ይሁንና ኢትዮጵያ ቼክ በምስሉ ላይ ባደረገው ማጣራት ምስሉ ኤርትራ ውስጥ የተነሳ እንዳልሆነ አረጋግጧል።
ምስሉ በመጀመርያ የተጋራው ልክ የዛሬ አመት ገደማ ‘African’ በተባለ እና ከ480 ሺህ በላይ ተከታታዮች ባሉት የትዊተር (ኤክስ) አካውንት ነበር (ሊንክ: https://x.com/i/status/2018940069969555640)
በተመሳሳይ ናይጄሪያዊው አክቲቪስት ‘Awoko Kwara’ ምስሉ በናይጄርያዋ ዮሩባላንድ ግዛት ውስጥ በምትገኘው ኢባዳን ከተማ ውስጥ ባለፈው አመት የተነሳ መሆኑን ጠቅሷል (ሊንክ: https://www.facebook.com/share/p/1C7UxJUYwC/)
በተመሳሳይ በርካታ የናይጄርያ ታዋቂ ግለሰቦች እና ፖለቲከኞች ምስሉን በማጋራት እና ምስሉ ኢባዳን ውስጥ እንደሆነ በመግለፅ ከተማዋ ልማት እና ፅዳት እንደሚያስፈልጋት አስተያየት ሲሰጡ ተመልክተናል።
ከሌላ ቦታ ተወስደው ካለማረጋገጫ የሚለጠፉ ምስሎች ለሀሰተኛ መረጃ ስለሚያጋልጡን ጥንቃቄ እናድርግ።
ኢትዮጵያ ቼክ
ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ
ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::





