ወደ ትግራይ ክልል ተቋርጠው የሚገኙ የአየር በረራዎች በነገው እለት ይጀምራሉ በሚል የተሰራጨው መረጃ የተሳሳተ ነው

ጥር 23፣ 2018
ወደ ትግራይ ክልል የሚደረጉ መደበኛ የአየር በረራዎች ከባለፈው እሮብ ማለትም ከጥር 20/2018 ዓ.ም ጀምሮ ተቋርጠው እንደሚገኙ ይታወቃል።
“ከበላይ አካል በመጣ ትዕዛዝ ነው” በተባለለት በዚህ የበረራ ስረዛ በርካቶች ከጉዞ እንደተስተጓጎሉ መረጃውን ቀድሞ ይዞ የወጣው መሠረት ሚድያ የዘገበ ሲሆን አንዳንድ ነዋሪዎች እና የአለም አቀፍ ድርጅቶች ሰራተኞች ከክልሉ ለመውጣት ጥድፊያ ላይ እንዳሉ ታውቋል።
ከዚህ ጋር በተያያዘ አንዳንድ የማህበራዊ ሚድያ ገፆች እና አካውንቶች የተቋረጠው በረራ ከነገ ቅዳሜ ጀምሮ እንደሚቀጥል መረጃ ለህዝብ እያጋሩ እንደሆነ ተመልክተናል።
ለምሳሌ ‘Angesom Abreha’ በሚል ስም የሚታወቅ እና ከ92 ሺህ በላይ ተከታታዮች ያሉት የፌስቡክ ገፅ ከጋዜጠኛ እንደሰማው በመግለፅ ያጋራው ይህ የተሳሳተ መረጃ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ በመቶዎች የሚቆጠሩ ግብረ-መልሶችን እና አስተያየቶችን አስተናግዷል።
ኢትዮጵያ ቼክ በዚህ ዙርያ የኢትዮጵያ አየር መንገድ እና የመንግስት ምንጮቹን ያነጋገረ ሲሆን በነገው እለት ወደ ትግራይ ክልል የሚደረግ በረራ እንደሌለ አረጋግጠዋል።
“ነገ ቅዳሜ በረራ እንደሌለ ማረጋገጥ እችላለሁ፣ እሁድ ወይም ከዛ በኋላ ስላሉት ቀናት አሁን ላይ በእርግጠኝነት መናገር ባልችልም በቅርብ ቀናት ይጀመራል የሚል ግምት የለኝም” በማለት ስሜ አይጠቀስ ያሉት ምንጫችን ተናግረዋል።
ሌላ አንድ ለኢትዮጵያ ቼክ መረጃ ያጋሩ የመንግስት ሀላፊም በረራው በነገው ዕለት አረጋግጠዋል።
ነገ እና ከነገ ወዲያ ለሚደረጉ በረራዎች እስከ ቅርብ ሰአታት ድረስ ትኬት በኢትዮጵያ አየር መንገድ ድረ-ገፅ ሲሸጥ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ። የፈረንሳዩ የዜና ወኪል ኤ ኤፍ ፒ (AFP) ወደ ትግራይ የሚደረጉ በረራዎች የተሰረዙት በክልሉ አዲስ በተቀሰቀሰ ግጭት እና የፀጥታ ስጋት መሆኑን መስማቱን በትናንትናው ዕለት ዘግቧል።
ኢትዮጵያ ቼክ!
ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ
ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::





