የአርብ ሳምንታዊ ዳሰሳ፡ ባለፉት አራት አመታት የጥላቻ ንግግርና የሐሰተኛ መረጃ ስርጭቶች በጎላ መልኩ እየታዩ መምጣታቸው ተገለጸ
መጋቢት 1፣ 2015 ዓ.ም
- የፍትሕ መጽሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ከተከሰሰበት የሀሰተኛ መረጃ ማሰራጨት ወንጀል በነጻ መሰናበቱን ኢትዮጵያ ኢንሳይደር ረቡዕ እለት ዘግቧል። ጋዜጠኛው በነጻ የተሰናበተበትን ፍርድ የሰጠው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አንደኛ የጸረ ሽብር እና ህገ መንግስታዊ ችሎት መሆኖም በዘገባው ተጠቅሷል። ጋዜጠኛ ተመስገን ነጻ የተባለው “ወታደራዊ ጉዳዮች” በሚል ርዕስ ስር በ2012 ዓ.ም እና “መከላከያ ተቋማዊ ወይስ ኔትዎርክ” በሚል ርዕስ ስር በ2014 ዓ.ም በፍትሕ መጽሔት ከታተሙ ጽሁፎች ጋር በተያያዘ ከቀረቡበት ክሶች መሆኑ ተገልጿል። ፍርድ ቤቱ ለክሱ መነሻ የሆኑትን ጽሁፎች በልዩ ሁኔታ የሚታለፉ እና ህትመቱን የተጠቀመውም የጥላቻ መረጃ ለማሰራጨት ሳይሆን ለዜና ዘገባ መሆኑን በመገንዘብ በነጻ እንዲሰናበት መወሰኑን ኢትዮጵያ ኢንሳይደር በዝርዝር ባቀረበው ዘገባ አስነብቧል።
- ቱኒዚያው ፕሬዝደት ኬይስ ሰዒድ ከስደተኞች አንጻር ተናገሩ የተባለውን የጥላቻ ንግግር ተከትሎ የአለም ባንክ (World Bank) በሀገሪቱ የሚተገብራቸውን የድጋፍ መርሐ-ግብሮች እንዲገቱ መወሰኑን ኤኤፍፒ በሳምንቱ መጀመሪያ ዘግቧል። የፕሬዝደንት ኬይስ ሰዒድ ንግግር “ዘርተኮር ጥቃት ብሎም ግጭት የሚቀሰቅስ ነው” ሲሉ የባንኩ ፕሬዝደንት ስለመናገራቸውም ኤኤፍፒ አስነብቧል። ፕሬዝደንት ኬይስ ሰዒድ ከሰሀራ በስተደቡብ የመጡ ፍልሰተኞችን በወንጀለኝነት እንዲሁም የስነ-ህዝብ ምጣኔን በማዛባት የከሰሱበትን ንግ ግር ተከትሎ የአፍሪካ ህብረትን ጨምሮ በርከት ያሉ ተቋማት የውግዘት መግለጫ ማውጣታቸው ይታወቃል።
- የጥላቻ ንግግርና ሐሰተኛ መረጃ ስርጭት ባለፉት አራት ዓመታት ውስጥ በጎላ መልኩ እየታየ የመጣ መሆኑን እና በኢትዮጵያ ለታዩ ችግሮች መፈጠርም መነሻ እየሆነ የነበረ መሆኑን የሰላም ሚንስቴር ዴኤታ ዶ/ር ስዩም መስፍን በሳምንቱ አጋማሽ ተናግረዋል። ሚንስትር ዴኤታው ይህን የገለጹት የሰላም ሚኒስቴር በጥላቻ ንግግር እና ሐሰተኛ መረጃ ስርጭት አዋጅ ዙሪያ ለምሁራን፣ ለሚድያ አካላት፣ ለማኅበረሰብ አንቂዎች እና ታዋቂ ግለሰቦች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ለመስጠት ባሰናዳው መድረክ ላይ ባደረጉት ንግግር ነው። ዶ/ር ስዩም “የጥላቻ ንግግር ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፍ መጥፎ ጠባሳ በማኅበረሰብ ላይ ጥሎ በማለፍ ከጦርነትም የከፋ ነው” ሲሉም ተደምጠዋል።
በዚህ ሳምንት ያቀረብናቸው መረጃዎች እና የቴሌግራም ሊንኮቻቸው:
– በሰኞ መልዕክታችን “ዜጎች ያልተገደበ መረጃ እንዲያገኙ ማድረግ ለሀሠተኛ መረጃ የመጋለጥ እድላቸውን ይቀንሳል” በሚል ርዕስ ጽሁፍ አጋርተናል: https://t.me/ethiopiacheck/1892
– በቦረና ዞን ከተከሰተው ድርቅ ጋር በተያያዘ የተሰራጨም ፎቶም አጣርተናል:
https://t.me/ethiopiacheck/1893
https://t.me/ethiopiacheck/1894
– ከሰሞኑ በማህበራዊ ሚዲያ በመጋራት ላይ ስለሚገኝ የማጭበርበሪያ ዘዴም ፍተሻ አድረገናል: https://t.me/ethiopiacheck/1899
በተጨማሪም የተለያዩ የሚዲያ አጠቃቀም ንቃትን ከፍ የሚያደርጉ በቪዲዮ የተደገፉ መልዕክቶችን አጋርተናል:
https://t.me/ethiopiacheck/1895
ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ
ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::