በአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትረምፕ እና በአምባሳደር ብናልፍ አንዱአለም መገናኘት ዙርያ ኢቢሲ ያሰራጨው የተሳሳተ መረጃ

ሰኔ 20፣ 2017
የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) ‘የኢትዮ-አሜሪካ ግንኙነት ከየት ወዴት?’ የሚል አንድ መረጃ በዛሬው እለት ለህዝብ ማቅረቡን ተመልክተናል።
በመረጃው ላይ የሕግ ምሁር እና የኢትዮጵያ እና አሜሪካን ግንኙነትን በቅርበት ከሚከታተሉ ሰዎች አንዱ ናቸው የተባሉት ፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያም የተባሉ ግለሰብ አስተያየት ሰጥተው ነበር።
ፕሮፌሰሩ አሁን ስላለው የኢትዮጵያ እና የአሜሪካ ግንኙነት ተጠይቀው ሲመልሱ ግንኙነቱ መሻሻሉን ጠቅሰው ለዚህም ማሳያ ይሆን ዘንድ በአሜሪካ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ከፕሬዚዳንት ትራምፕ ጋር በነጩ ቤተ መንግሥት መገናኘታቸውን እንደ ዋነኛ ማሳያ ጠቅሰዋል፡፡
“አንድ የውጭ ሀገር አምባሳደር የሥራ ደብዳቤውን ሲያቀርብ አልፎ አልፎ ፕሬዚዳንቶችን ሊያገኝ ይችላል” ያሉት ፕሮፌሰሩ የአምባሳደር ብናልፍ ከፕሬዚዳንት ትራምፕ ጋር መገናኘት ግን ያልተለመደ እና በጣም ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን አውስተዋል፡፡
ሌላው የሁለቱ ሀገራት በዘላቂነት እየተሻሻለ መምጣት ማሳያው የአሜሪካ ማሪን ኮርፕስ ጄኔራል እና አፍሪኮም አዛዥ የሆኑት ጄነራል ማይክል ላንግሌይ የኢትዮጵያ ጉብኝት መሆኑን ፕሮፌሰር ዓለማየሁ ተናግረዋል፡፡
በነዚህ ሁለት ጉዳዮች ላይ ኢትዮጵያ ቼክ ማጣራት አድርጓል።
በመጀመርያ የተመለከትነው ፕሬዝደንት ትረምፕ እና አምባሳደር ብናልፍ የነበራቸው መገናኘት ያልተለመደ እንደሆነ የቀረበው መረጃን ነው።
“በአለም ዙርያ እንደሚደረገው ሁሉ በአሜሪካ የሚመደቡ አምባሳደሮችም ሰብሰብ ብለው የሀገሪቱን ፕሬዝደንት በማግኘት የሹመት ደብዳቤያቸውን ማቅረብ የተለመደ ነው” ብለው ለኢትዮጵያ ቼክ ያስረዱት አንድ ስሜ አይጠቀስ ያሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባልደረባ ናቸው።
“የአሜሪካ እና የኢትዮጵያ ግንኙነት ጥሩ የሚባል ደረጃ ላይ ይገኛል። ይህን ለማስረዳት ግን የተለመደ የዲፕሎማቲክ አሰራርን ልዩ እና ያልተለመደ አርጎ ማቅረብ አሳሳች ነው” በማለት አስረድተዋል።
አክለውም ፕሬዝደንት ትረምፕ ከሰሞኑ የህዳሴ ግድብን ፋይናንስ ያረገችው ሀገራቸው አሜሪካ መሆኗን እንዲሁም የህዳሴ ግድን የናይል ወንዝ ፍሰትን ይቀንሳል የሚል መረጃ ማጋራታቸው ስጋትን በተወሰነ መልኩ ፈጥሯል ብለዋል።
አምባሳደር ብናልፍ አንዱአለም ይፋዊ የሹመት ደብዳቤያቸውን ይዘው አሜሪካ በመግባት ስራ የጀመሩት እ.አ.አ በጃንዋሪ 3/2025 ዓ/ም መሆኑን የአሜሪካው ውጭ ጉዳይ ቢሮ (ስቴት ዲፓርትመንት) መረጃ ያሳያል (ማስረጃ: https://www.state.gov/office-of-the-chief-of-protocol/diplomatic-corps-order-of-precedence-and-dates-of-presentation-of-credentials)
ይሁንና ፕሬዝደንቱ እያንዳንዱ አምባሳደር ስራ በጀመረበት ቀን ማግኘት ስለማይችሉ ሰብሰብ አድርገው በቅርቡ እንዳገኙ እና ከሰሞኑ አምባሳደር ብናልፍን ጨምሮ የ11 ገደማ ሀገራት አምባሳደሮችን ሹመት እንደተቀበሉ ታውቋል።
በዚህም መሰረት “አንድ የውጭ ሀገር አምባሳደር የሥራ ደብዳቤውን ሲያቀርብ አልፎ አልፎ ፕሬዚዳንቶችን ሊያገኝ ይችላል… የአምባሳደር ብናልፍ ከፕሬዚዳንት ትራምፕ ጋር መገናኘት ያልተለመደ ነው” በማለት በፕሮፌሰሩ የቀረበው መረጃ የተሳሳተ መሆኑን ማየት ይቻላል።
በሌላ በኩል የአሜሪካ ማሪን ኮርፕስ ጄኔራል እና አፍሪኮም አዛዥ የሆኑት ጄነራል ማይክል ላንግሌይ የኢትዮጵያ ጉብኝት ልዩ መሆኑን ፕሮፌሰሩ ገልፀዋል።
ይህም በተመሳሳይ መልኩ በኢትዮጵያ ብቻ የተደረገ ልዩ ጉብኝት ሳይሆን ጄነራል ማይክል ላንግሌይ ከኢትዮጵያ ቀደም ብለው በሶማሊላንድ እና ጂቡቲ ጉብኝት አድርገው እንደነበር የአሜሪካ አፍሪካ ኮማንድ (AFRICOM) ይፋዊ መረጃ ያሳያል (ማስረጃ: https://www.africom.mil/pressrelease/35879/commanders-visit-to-east-africa-reiterates-security-partnerships-cooperation)
ኢትዮጵያ ቼክ!
ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ
ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::
