ይህ ምስል በእስራኤል ወታደር እየሰለጠኑ ያሉ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላትን አያሳይም

ህዳር 8፣ 2018

በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መሀል ያለውን የግንኙነት መሻከር መነሻ በማድረግ የሁለቱ ሀገራትን የጦር እንቅስቃሴ ‘ያሳያሉ’ በሚል የምስል እና ቪዲዮ መረጃዎች መጋራት ከጀመሩ ሰነባብቷል።

በዚህ ረገድ በሰው-ሰራሽ አስተውሎት (AI) የተፈበረኩ የከባድ ጦር መሳሪያ ምስሎች እንዲሁም ትክክለኛ ምስሎች ላይ አዲስ ይዘቶችን በመጨመር የሚጋሩ ሀሰተኛ እና አሳሳች መረጃዎችን በየእለቱ መመልከትም የተለመደ ሆኗል።

ኢትዮጵያ ቼክ ይህን ጉዳይ በተመለከት በአንዳንድ ማህበራዊ ትስስር ገጾች ላይ ክትትል ሲያደርግ የቆየ ሲሆን አንዳንድ ገጾች እና አካውንቶች ተከታታይነት ባለው መልኩ በሰው-ሰራሽ አስተውሎት የተፈበረኩና ይዘታቸው የተቀየረ ምስሎችን በመጠቀም ሀሰተኛ እና አሳሳች መረጃዎችን እየጋሩ እንደሚገኙ ተመልክቷል።

ከነዚህ የማህበራዊ ትስስር ገጾች መካከል ደግሞ ‘The Leak Line’ የሚል ስም እና ከ58 ሺህ በላይ ተከታዮች ያለሉት የፌስቡክ ገጽ ይገኝበታል።

ለአብነት ያህል ይህ ገጽ ስክሪን ቅጂው የሚታየውን ምስል “እስራኤል የኢትዮጵያን መከላከያ ሰራዎት እያሰለጠነች ነው” ከሚል ጽሁፍ ጋር ከቀናት በፊት አጋርቷል።

ይህ ገጽ ዋናዉን ምስል ከኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት የፌስቡክ ገጽ የወሰደ ሲሆን ትክክለኛ ምስሉ ላይ “የእስራኤል ወታደር” የሚመስል ሰው ምስል በመጨመር ምስሉ አዲስ ይዘት እንዲኖረው አድርጓል።

በመቀጠልም አዲስ ይዘት የተጨመረበትን ምስልም “እስራኤል የኢትዮጵያን መከላከያ ሰራዊት እያሰለጠነች ነው” ከሚል ጽሁፍ ጋር አጋርቷል።

ይሁን እንጂ ከኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት የፌስቡክ ገጽ የተወሰደው ትክክለኛ ምስል በአማራ ክልል ኦሮሞ ብሄረሰብ ዞን ዉስጥ በመከላከያ ስልጠና የተሰጣቸዉ የሚሊሻ አባላት ናቸው፡ https://www.facebook.com/share/p/1BULAkjvUq/?mibextid=wwXIfr

ይህን ምስል እንደ ምሳሌ አነሳን እንጂ ይህ ገጽ በተመሳሳይ መልኩ ከሌላ ቦታ በመውሰድና ይዘታቸውን በመቀየር እነዲሁም በሰው-ሰራሽ አስተውሎት አዳዲስ የወታደራዊ ጦር መሳርያ ምስሎችን በመስራት ከአውድ ዉጭ ያጋራቸዉ መረጃዎች በርካታ ናቸው።

በመሆኑም ታማኝ ባልሆኑ የመረጃ ምንጮች የሚጋሩ አጠራጣሪ መረጃዎችን ከማመናችን እና መልሰን ከማጋራታችን በፊት ተገቢዉን ማጣራት እናድርግ።

ኢትዮጵያ ቼክ!

ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ

    ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::