ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ በአያቶላህ አሊ ኻሜኒ ሞት ሀዘናቸዉን እንደገለጹ ተደርጎ የተሰራጨው ስክሪን ቅጂ ሀሰተኛ ነው

የካቲት 24፣ 2018
/ኢትዮጵያ ቼክ/- ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ በኢራኑ መንፈሳዊ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ሞት ሀዘናቸዉን እንደገለጹ የሚያሳይ ስክሪን ቅጂ (screenshot) በማህበራዊ ትስስር ገጾች እየተጋራ ይገኛል።
ይህ ስክሪን ቅጂ “በወንድሜ አያቶላህ አሊ ኻሚኒ ሞት የተሰማኝን ጥልቅ ሀዘን እገልጻለሁ። ኻሚኒ ላለፉት 40 አመታት ኢራንን በለዉጥ ጎዳና የመሩ ብርቱ ሰው ናቸዉ” የሚል መልዕክት ይዟል። በተጨማሪም “ለቤተሰቦቻቸው፣ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው እንዲሁም ለመላ ኢራናዊያን መጽናናትን እመኛለሁ” ይላል።
በርካታ የኢትዮጵያ ቼክ ተከታዮችም የስክሪን ቅጂዉን ትክክለኛነት እንድናጣራ ጥቆማቸዉን አድርሰዉናል።
ኢትዮጵያ ቼክ የዚህን ስክሪን ቅጂ ትክክለኛነት ለማጣራት በመጀመርያ መልዕክቱ የጠ/ሚሩ የማህበራዊ ሚድያ ገፆች ላይ እንዳለ ቅኝት አድርጎ እንደዚህ አይነት መልዕክት እንደሌለ ተመልክተናል።
በሁለተኛነት ይዘታቸው የተቀየሩ ፎቶዎችን ለመመርመር የሚረዳውን ‘Fotoforensics’ ድረ-ገጽን ተጠቅመናል።
ይህ ድረ-ገጽ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፌስቡክ ስም የሚገኝበት የስክሪን ቅጂዉ ክፍል የተነካካ ወይም በኮፒ ፔስት (Copy and Paste) ይዘቱ የተቀየረ እንደሆነ አሳይቷል።
በሌላ በኩል በስክሪን ቅጂዉ ላይ የሚገኘው ይዘቱ የተለጠፈበትን ጊዜ የሚያሳይ መግለጫ (Time Stamp) የፊደላት ቅርጽ (Font) ስህተት እንዲሁም ከበስተቀኙ የሚገኘው የግላዊነት ቅንብር የአለም ምስል (Public Privacy Setting Globe Icon) ደግሞ የአቀማመጥ ግድፈት (Misalignment) ያለበት መሆኑንም ተመልክተናል።
በተጨማሪም የስክሪን ቅጂዉ ዋና ይዘት ጽሁፍም በተመሳሳይ መልኩ የተለያዩ ግድፈቶች ያሉበት ሲሆን ይህም በቅንብር የተሰራ እንደሆነ የሚጠቁም ነው።
በመጨረሻም፣ መረጃው በተለጠፈ በ14 ደቂቃ ውስጥ 44,500 ግዜ ሪአክሽን እንዳገኘ ማሳየቱ በጠ/ሚሩ የፌስቡክ ገፅ ላይ ያለውን መስተጋብር እንደማያሳይ አይተናል።
በሌላ በኩል ግን ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ ኢራን በኩዌት ላይ የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ ከኩዌት ልዑል አልጋ ወራሽ ጋር በስልክ መወያየታቸው እንዲሁም በአገሪቱ ላይ የሚፈጸም ጥቃትን በጽኑ ማውገዛቸውን የኩዌት የዜና ወኪል ዘግቧል።
ኢትዮጵያ ቼክ
ወቅታዊ መረጃዎችን ቀጥታ በኢሜልዎ ለማግኘት ይመዝገቡ
ያቀረቡትን የግል መረጃ በግላዊ መመሪያችን መሠረት እንጠብቃለን::





